“ይህ አስከፊና አደገኛ ሁኔታ ለዜጎች ህይወት መጥፋት ፣ ጉስቁልናና የወደፊት ተስፋ መታጣት ምክንያት ሆኗል” ያሉት ዶክተር ደብረፅዮን በዚህ ከቀጠለ በአገሪቱ አንድነትና ህገ-መንግስታዊ ስርዓት ላይ የከፋ አደጋ እንዳይከሰት ስጋት መፍጠሩንም አስረድተዋል።
“እየታየ ያለውን ከፍተኛ ስጋትም ሁላችንም ተባብረን በመታገል ህዝቦቻችን የሚፈልጉትን ሰላም ፣ ልማትና ዴሞክራሲ ለማስፈን ችግር የሚፈጥሩ አካላትን በብቃት መመከት አለብን” ብለዋል ።
“አሁን በአገሪቱ በስፋት እየተከሰቱ ያሉትን ቸግሮች ህገ-መንግስቱን ካለማክበርና የህግ የበላይነትን ካለማረጋገጥ የሚመነጩ ናቸው” ብለዋል።
እየተፈጠሩ ላሉት ችግሮች ምክንያቱ የፌዴራል ስርዓቱ እንደሆነ ለመግለጽ የሚሞክሩ ሃይሎች መኖራቸውን ገልጸው የብሄር ግጭቶች፣ማንነት ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶች መበራከታቸው በፌዴራል ስርዓት በመመራታችን ሳይሆን ህግና ህገ-መንግስትን በአግባቡ ማስከበር ባለመቻሉ የመጣ እንደሆነም ተናግረዋል።
“የውጭ ጠላቶቻችን የሀገራችን መዳከም ብቻ ሳይሆን መበታተን የግድ አስፈላጊ ነው ብለው እየተረባረቡ ይገኛሉም” ብለዋል ።
በመድረኩ ላይ “ህገ-መንግስትና ህገ-መንግስታዊ ስርዓት በኢትዮጵያ” በሚል ርዕስ የመወያያ ጽሑፍ ያቀረቡት ዶክተር መንበረጸሐይ ታደሰ በበኩላቸው አራተኛ ህገ-መንግስት የሆነው የአሁኑ ህገ-መንግስት የተረቀቀው በኢትዮጵያ ብሄሮች፣ብሄረሰቦችና ህዝቦች ሰፊ ውይይት ተደርጎበት መሆኑን ተናግረዋል።
ህገ-መንግስቱ ከመጽደቁና ተግባራዊ ከመደረጉ በፊትም በ22 ሺህ ቀበሌዎች ውስጥ በህዘብ ሰፊ ውይይት የተደረገበት ከመሆኑም ባለፈ፣በዓለም አቀፍ መስፈርት መሰረት የህገ-መንግስት አርቃቂ ኮሚሽን ተቋቁሞና በወቅቱ ለነበረው የተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ እንደነበርም አስታውሰዋል።
ህገ-መንግስቱ በተለይ በብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ውስጥ የነበሩ መሰረታዊ የማንነት፣የሰላም እጦትና የመሬት ባለቤትነት ጥያቄዎችን የመለሰ መሆኑንም አስረድተዋል።ለሁለት ቀናት በሚካሔደው መድረክ ላይ “ህብረ-ብሄራዊ ፌደራላዊ ስርዓት በኢትዮጵያ”፣”የህግ የበላይነትና ሰላምና ደህንነት በኢትዮጵያ” ና “ምርጫ 2012 በኢትዮጵያ” በሚሉ-ርእሰ ጉዳዮች ላይ በምሁራን ጽሁፎች ቀርበው ውይይት እንደሚደረግባቸው ይጠበቃል።
በመድረኩ ላይ ክልላዊና ሀገራዊ የፖለቲካ ፓርቲዎች ፣ የሃይማኖት አባቶችና ምሁራን እየተሳተፉ ይገኛሉ።